በጦርነቱ ጉዳት ለደረሰባቸው አካባቢዎች የችግኝና የዘር ድጋፍ ተደርገ

የጎንደር ዩኒቨርሲቲ አሸባሪውና ዘራፊው የትግራይ ወራሪ ሀይል በጦርነቱ ወቅት ያደረሰውን ስነ-ልቦናዊና ቁሳዊ ውድመት ወደ ነበረበት እንዲመለስና በአካባቢው ማሕበረሰብ መነቃቃትን ለመፍጠር በርካታ የመልሶ ማቋቋም ስራዎችን ሲያከናውን ቆይቷል፡፡ በጦርነቱ ወቅት ጉዳት ደርሶባቸው ከነበሩ አካባቢዎች መካከል አንዱ በሆነው የዋግኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞንም በርካታ ድጋፎች ተደርገዋል፣ ስልጠናዎች ተሰጥተዋል እንዲሁም ጥናቶች ተካሂደዋል፡፡

የግብርናና አካባቢ ሳይንስ ኮሌጅም በበኩሉ በዞኑ ለሚገኙ የቀበሌ፣ የወረዳና የዞን የግብርና ባለሙያዎች እንዲሁም አመራሮች የስነ ልቦናና የሙያ አቅም ማጎልበቻ ስልጠና ሰጥቷል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ከሰብል ልማት፣ ከአትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም ከተፈጥሮ ሀብትና ደን ልማት አኳያ የዳሰሳ ጥናት በማድረግ ለአካባቢው ምቹ የሆኑና የተሻለ ምርት ሊሰጡ የሚችሉ የሰብል የአትክልት ዘሮችንና የማዳበሪያ ድጋፍ መደረጉን የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የግብርናና አካባቢ ሳይንስ ኮሌጅ የማህበረሰብ አገልግሎት አስተባባሪ አቶ በየነ ደርሶ ገልጸዋል፡፡ በኮሌጁ በአጠቃላይ ከ750 ሺህ ብር በላይ የሚያወጣ የአትክልትና ፍራፍሬ ዘርና ችግኝ፣ የደን ልማት ዘርና ቁሳቁስ፣ የሰብል ዘሮች (የጤፍ፣ ማሽላና ስንዴ) እና የማዳበሪያ ድጋፍ መደረጉን አቶ በየነ ጨምረው ተናግረዋል፡፡ በተመሳሳይ ነሐሴ 9 እና 10/2014 ዓ.ም በሰቆጣ ወረዳ ወለህ እና ፍቅረ ሰላም ቀበሌዎች ለሚገኙ አርሶ አደሮች የአቦካዶና የብርቱካን ችግኞች ስርጭት ተደርጓል፡፡

ከስርጭቱ በተጨማሪም የግብርናና አካባቢ ሳይንስ ኮሌጅ የሆርቲ ካልቸር መመምህርና የትምህርት ክፍሉ ሃላፊ በሆኑት በአቶ ፈንታሁን አስራት አማካኝነት ሙያዊ ገለጻ ከተደረገ በኋላ የቀበሌና የወረዳ የግብርና ባለሙያዎችና አመራሮች በተገኙበት ሞዴል የችግኝ ተከላ ተካሂዷል፡፡ በእለቱ በዩኒቨርሲቲው በድጋፍ መልክ ለዞኑ የተሰጠና በወለህ ቀበሌ በሙከራ ላይ የሚገኝ የስንዴ ሰብል ጉብኝትም ተደርጓል፡፡

በዋግኽምራ ብሄረሰብ አስተዳደር ዞን የግብርና መምሪያ ኃላፊ የሆኑት አቶ አዲስ ወልዴ ዞኑ በተቸገረበት ወቅት ከማንም በላይ የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ፈጥኖ በመድረስ በተለይ ባለሙያዎች ከነበሩበት ስነ-ልቦናዊ ጫና በፍጥነት ወጥተው ወደ ልማት እንዲገቡ ስልጠና በመስጠት ላደረገው ከፍተኛ አስተዋፅኦና በጦርነቱ ምክንያት ለተከሰተው የዘር እጥረት ላደረገው ድጋፍ ያላቸውን ምስጋና ገልፀው ዩኒቨርሲቲው ወደፊትም ዞኑ ካለው የቦታ ርቀት አንፃር ባለሙያዎች በክረምትም ይሁን በተከታታይ መርሀግብሮች ራሳቸውን ለማሳደግ ከፍተኛ ችግር ስለሚገጥማቸው ለባለሙያዎች የትምህርት እድል በመስጠትና በመሰል ድጋፎችም ከጎናቸው እንዲሆን መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡ የችግኝ ድጋፍ ያገኙት የሰቆጣ ወረዳ ነዋሪ የሆኑት አቶ ወርቁ ጸሀዩ የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ላደረገላቸው ድጋፍ አመስግነው ወደፊትም የሌሎች ችግኞች ድጋፍ ቢደረግልን ሲሉ ሀሳባቸውን ሰጥተዋል፡፡
የጎንደር ዩኒቨርሲቲ በሁሉም መስኮች የቦታ ርቀት ሳይበግረው በሁሉም አካባቢዎች ማህበረሰቡ ያለበትን ችግር በመረዳት፣ በጥናት በመለየትና በማረጋገጥ ለማህበረሰቡ የተሻለ ህይወት እየተጋ ይገኛል፡፡

Start Time

12:00 am

August 19, 2022

Finish Time

12:00 am

October 20, 2023